ዜና
በበጎነት መንደር፤ ተጨማሪ የበጎነት ተግባር!
07 ግንቦት 2018
ማህበራዊ ፍትህን የምናነግስበት አንዱ የተስፋ ብርሃን የምገባ ፕሮግራማችን፣ ዛሬ በልደታ ክፍለ-ከተማ ለክፍለ-ከተማው 3ኛ የሆነ 29 ኛውን የተስፋ ብርሃን ምገባ ማዕከል ገንብተን ስራ አስጀምረናል።
በገነባነው 492 ቤቶች ውስጥ ለሚኖሩ 2,460 ለሚሆኑ ነዋሪዎቻችን እፎይታ በሆነው በተለይም በርካታ አረጋውያን፣ ለማህበራዊ ችግር የተጋለጡና ድጋፍ ለሚሹ ወገኖቻችን እንዲሁም ለልማት ተነሺዎች በሚኖሩበት የበጎነት መንደር ውስጥ ድጋፍ ለሚገባቸው ወገኖች ዛሬ ምገባ ያስጀመርንበት የምገባ ማዕከል ተጨማሪ የበጎነት ስራ ነው ።
ንፁህ፥ ትኩስ ምግብ በቀን አንድ ጊዜ የሚቀርብባቸው በሁሉም ክፍለ ከተማ 29 የምገባ ማዕከላት ውስጥ መመገብ ስለሚቻል፤ ለችግር የተጋለጡ ወገኖቻችን ምግብ ፍለጋ ወደ ጎዳና የሚያስወጣ ምክንያት በከተማችን ስለሌለ፤ በማዕከላቱ በመገኘት መመገብ ትችላላችሁ። በዚህ የበጎነት መንደር የስራ እድል የተፈጠረባቸው የእንጀራ መጋገሪያ ማዕከል፣ የልብስ ስፌት፣ የፀጉር ስራና የልጆች መጫወቻ ለነዋሪዎቹ ሌላኛው የእፎይታ ምንጭ ናቸው።
ሁሌም ማህበራዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ ያለው ዳሽን ባንክ ጥሪአችንን ተቀብሎ ለማዕከሉ ግንባታ እና በቀጣይም ለመመገብ ላደርገልን ድጋፍ በራሴና በተጠቃሚዎች ስም ክልብ እመሰግናለሁ።
ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ከንቲባ አዳነች አቤቤ